የምስራቅ ፖሊ ቴክኒክ ኮሌጅ አለም አቀፍ መመዘኛዎች በማሟላት ISO ሽልማት ተሰጠው ።
የካቲት 02/06/2018
በእውቅና ስነ -ስርዓቱ መድረክ ላይ በመገኘት ንግግር ያደረጉት በቢሮ ኃላፊ ደረጃ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ሥራና ክህሎት ቢሮ የዉጤት ተኮር እና ልማት ዘርፍ ኃላፊ ክብርት ወ/ሮ ዳግማዊት ግርማ ፣ እንደገለፁት የቴክኒክና ሙያ ትምህርትና ስልጠና ዘርፍ ብቁ፣ ሥራ ፈጣሪና ለስራ ዝግጁ የሆኑ ሙያተኞችን በማፍራት የሀገራችን የኢኮኖሚ እድገት በማፋጠን ረገድ የበኩሉን ከፍተኛ ሚና እየወጣ ይገኛል ብለዋል።
በዛሬው እለት ለኮሌጁ የተሰጠዉ እውቅና ተቋማት የተቋም አስተዳዳርና አመራር እንዲያጠናክሩ ፣ ስልጠናን ከስራ ገበያና ኢንዱስትሪ ፍላጎት ጋር ማጣጣም እንዲችሉ ፣ የስልጠናና ምዘና ሂደቶችን እንዲገመገሙ ፣ የሰልጣኞችን እርካታና የአጋሮች እምነትን እንዲያሳድጉ ፣ ግልጸኝነትና ተጠያቂነት ስርአት በማጠናከር ከፍተኛ አስተዋጽኦ የሚያበረክት እንደሆነ ገልጸው ለዚህ ሸልማት በመብቃታችሁ እንኳን ደስ አላችሁ ብለዋል።
የምስራቅ ፖሊ ቴክኒክ ኮሌጅ ዋና ዲን የሆኑት አቶ ዮሀንስ ሁንዱማ በበኩላቸው የISO 21001: 2018 የትምህርት ተቋማት አስተዳደር ስርዓት ማረጋገጫ የምስክር ወረቀት አሰጣጥ ሰርቲፊኬት የምንቀበልበት ብቻ ሳይሆን ለተጠያቂነት፣ ለጥራት ያለን ቁርጠኝነት እና ቀጣይ ጉዞአችንን የምናሳድግበት ቀን ነዉ በማለት ለተገኘው ስኬት የጠንካራ አመራር እና የሁሉም ሰራተኞች ቁርጠኝነት ነዉ ሲሉ የእንኳን ደስ አላችሁ መልዕክት አስተላልፈዋል ።
የኢትዮጵያ የተስማሚነት ምዘና ዋና ዳይሬክተር መዓዛ አበራ(ኢንጂነር ) በበኩለቸዉ የስራ አመራር ስርዓቶችን በተቋማት ዉስጥ መተግባር ወጥ የሆነ አሰራር ስርዓት እንዲኖር ፤ እንዲሁም የት/ርት ተቋማት ላይና የሰልጣኞች ፍላጎት ለማሟላት፤ የተሻለ አፈጻጸም እንዲያመጡ፤ የትምህት ጥራት ለማስጠበቅ እና የሚሰጡ አገለግሎቶች አለም አቀፋዊ እውቅና እንዲኖራቸዉ የሚያስችሉ በመሆናቸዉ ፤ ለዚህ ስኬት ተግታችሁ በመስራታችሁ ይህ ዉጤት ሊመዘገብ ችልዋልና እንኳን ደስ ያላችሁ ብለዋል፡፡
በመድረኩ የስራና ክህሎት ቢሮ ከፍተኛ አመራሮች የኮሌጁ ማህበረሰብና ተጋባዥ እንግዶች ተሳታፊ ሆነዋል። በመርሃ ግብሩ ላይ ለስኬቱ የበኩላቸዉን አስተዋጽኦ ላበረከቱ አካላት የምስጋና እና የእዉቅና ሸልማት ተበርክቶላቸዋል፡፡
የምስራቅ ፖሊ ቴክኒክ ኮሌጅ መነሻዉን 1961 ልዑል አስፋዉ ወሰን አጠቃላይ 2ኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ከ1960 ዓ.ም ጀምሮ የቀለምና ሙያ ትምህርት በኋላም 1994 ወደ ቴክኒክና ሙያ ትምህርት ተቋም ተቀይሮ የተለያዩ ሙያተኞች በማሰልጠን ቆይተዉ ከ2002 ጀምሮ ከተቋምነት ወደ ፖሊ ቴክኒክ ኮሌጅ በመባል ከደረጃ 1 እስከ 5 የተለያዩ የሙያ አይነቶች እያሰለጠነ የሚገኝ ተቋም ነዉ።
.